ኢትዮጵያ ከህንድ ጋር በአምራች ኢንዱስትሪው ዘርፍ ያላትን ትብብር ለማጠናከር ትሻለች – ሚኒስትር ዴኤታ ሀሰን መሐመድ

ኢትዮጵያ ከህንድ ጋር በአምራች ኢንዱስትሪው ዘርፍ ያላትን ትብብር ለማጠናከር ፍላጎት እንዳላት የኢንዱስትሪ ሚኒስትር ዴኤታ አቶ ሀሰን መሀመድ ገለጹ።

ሚኒስትር ዴኤታው ከህንድ የኢንዱስትሪ ማህበር(Confederation of Indian Industry) ባለሀብቶች ጋር በጽህፈት ቤታቸው ተወያይተዋል።

ውይይቱ ባለሀብቶቹ በኢትዮጵያ የአምራች ኢንዱስትሪ ዘርፍ በሚሰማሩበት ሁኔታ ላይ ያተኮረ ነው።

ሚኒስትር ዴኤታው መንግስት የዜጎችን ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ እና የኢትዮጵያን ብልጽግና እውን ለማድረግ ለአምራች ኢንዱስትሪው ዘርፍ በልዩ ትኩረት እየሰራ እንደሚገኝ ገልጸዋል።

በዘርፉ ለሚሰማሩ የውጭ ኢንቨስተሮች ምቹ የኢንዱስትሪ የህግ ማዕቀፍ ከማዘጋጀት ጀምሮ በርካታ የኢንቨስትመንት አማራጮች መመቻቸታቸውን አመልክተዋል።

ኢትዮጵያ እና ህንድ በአምራች ኢንዱስትሪው ዘርፍ ያላቸው ትብብር መጠናከር ለኢንዱስትሪ እድገት እንዲሁም ለቴክኖሎጂና ለዕውቀት ሽግግር ከፍተኛ ሚና እንደሚጫወት ተናግረዋል።

ለሀገራቱ ዜጎች የህዝብ ለህዝብ ትስስርን ከመፍጠር ባሻገር በዓለም አቀፉ ገበያ የጎላ ድርሻ እንዲኖራቸው አስተዋጽኦ ያደርጋል ነው ያሉት።

ከህንድ የኢንዱስትሪ ማህበር የመጡት ባለሀብቶች ኢትዮጵያ ውስጥ በአምራች ኢንዱስትሪ ዘርፍ መዋዕለ ንዋይ ለማፍሰስ ምቹ ሁኔታዎች እንዳሉ ለመረዳት እንደቻሉ መግለጻቸውን ከሚኒስቴሩ የተገኘው መረጃ ያመለክታል።

ምንጭ፦ ኤፍ.ኤም.ሲ

Leave a Comment

Your email address will not be published. Required fields are marked *